07/01/2026
ለአንድ ወዳጃችን ልደት “እንኳን ተወለድክ” ለማለት ቃላት ይቸግሩናል። አንዳች አዲስ የፍቅር መግለጫ ፍለጋ ማኅበራዊ ገጾችን እናስሳለን፤ ከልባችን ስሜት ይልቅ በጥሩ ለዛ የቀረቡ ቃላትን እንመርጣለን። ዛሬ ግን የፍቅር ሁሉ ምንጭ፣ የሰማይና የምድር ፈጣሪ፣ የዓለም ሁሉ ቤዛ የሆነው የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ነው!
ለዚህ ድንቅ ዕለት ምዕመናን ሁሉ እንደ ሰባሰገል በብርሃን ተመርተው፣ በየአቅጣጫው ለምስጋና ተሰባስበዋል። “ቤዛ ኩሉ ዓለም ዮም ተወልደ” እያሉ ለማዜም፤ ገሚሱ ወደ ቅዱስ ላሊበላ አቅንቷል፣ ገሚሱ ደግሞ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በ”አእላፋት ዝማሬ” ተገኝቷል። በኋላም በየአብያተ ክርስቲያናቱ በማኅሌትና በቅዳሴ ተሳታፊ በመሆን፣ የክርስቶስን ልደት ባለቤቱ በሚወደውና በሚከብርበት መንገድ አክብረናል።
አንድን ሰው “እንኳን ተወለድክ” ስንለው ትንሹ የምስጋናችን መግለጫ የሚወደውን ነገር ማድረግ ነው። ለመሆኑ ለእግዚአብሔር ልደት ምን እናድርግለት ይሆን? እርሱስ በምን ደስ ይለው ይሆን? ትልቁ ስጦታችን በበጎ ምግባር የታጀበ የፍቅር ልብ ነው፤ እርሱ የቤተክርስቲያን አምባሳደሮች እንድንሆን ይሻል።
ይህ በየቦታው መገኘታችን መለያየት ሳይሆን የምስጋና ስፋት (ስፋተ-ስብሐት) ነው። በዚያች የቤተልሔም ምሽት መላእክት በሰማይ ሲዘምሩ፣ እረኞች በምድር ድምፃቸውን ሲያስተጋቡ የሰማዩ ዜማ የምድሩን ድምቀት አልሸፈነውም፤ ይልቁንም ሰማይና ምድር በአንድ ዜማ የልደቱን ብርሃን አበሰሩ እንጂ። ዛሬም በላሊበላ የሚወርደው ማኅሌትና በአደባባይ የሚሰማው ዝማሬ ምንጩ አንድ ነው— እርሱም ምስጋና ለእግዚአብሔር!
እኛም የዓለምን ግርግር ትተን ከመላእክቱ ጋር እንዲህ እንላለን፦
ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ” (ሉቃስ 2:14)
ስብሐት ለእግዚአብሔር ፤ ሰላምም ለሰው
እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ።
ሚክያስ ልየው | Mikiyas Liyew
አዲስ አበባ, ኢትዮጵያ | Addis Ababa,Ethiopia
ታኅሣሥ ፳፱-፳፻፲፰ ዓ.ም