15/08/2026
አዲስ አበባን እንደ ደሴት ማሰብ ከንቱ ቁዠት ነው፤ የሀሰት ፕሮፖጋንዳው ይቁም!
በማህበራዊ ሚዲያ ላይ አዲስ አበባን እና ኦሮሚያን እርስ በርስ ለማጋጨት ሆን ተብለው የሚነዙ የተሳሳቱ ትርክቶችን በስፋት እየተመለከትን ነው። ነገር ግን ሁላችንም በግልጽ ልንገነዘበው የሚገባው ትልቁ እውነታ፣ አዲስ አበባ ከኦሮሚያ ክልል ጋር ያላት ግንኙነት እጅግ ጥብቅ፣ የማይነጣጠል እና ተፈጥሯዊ መሆኑን ነው። አዲስ አበባን ከዙሪያዋ ካለው የተፈጥሮ ማህጸን ሙሉ በሙሉ ነጥሎ እንደ ደሴት ብቻዋን እንድትኖር ማድረግ ፈጽሞ የማይቻል እና ከተፈጥሮ ህግ ጋር የሚጋጭ ነው። ይህን ለማድረግ መሞከርም ሆነ እንደዚያ አድርጎ ማሰብ ከንቱ ቁዠት ነው።
ከተማዋ የእለት ተዕለት የምግብ ፍጆታዋን፣ የውሃ አቅርቦቷን፣ የግንባታ ጥሬ እቃዋን እንዲሁም የኢንቨስትመንት ፍላጎቷን የምታሟላው ከዚሁ ተፈጥሯዊ ጎረቤቷ ጋር በጥብቅ በመቀናጀት ነው። ላለፉት 35 አመታት የኦሮሚያ ክልል መንግስት መቀመጫ በመሆን፣ ህዝቡም በሰላም፣ በፍቅር እና በመከባበር አብሮ ኖሯል። ይህ የ35 ዓመታት ጤናማ አብሮነት ዛሬም ወደፊትም የሚቀጥል እንጂ፣ ማንም ፖለቲከኛ በፈጠረው የሀሰት ትርክት የሚፈርስ አይደለም።
ስለዚህ፣ ከተማዋን "ልትወረር ነው" ወይም "በሌላ ክልል ልትዋጥ ነው" በሚል የሚሰራጨው አፍራሽ እና የሀሰት ፕሮፖጋንዳ በአስቸኳይ መቆም አለበት። ህዝባችንም ኢትዮጵያን ለማፍረስ እና ወንድማማች ህዝቦችን ለማጋጨት ለሚሰሩ የጥፋት ሃይሎች የፈጠራ ወሬ በፍጹም ጆሮ መስጠት የለበትም። በእነዚህ ወገኖች የሚነዛው አሉባልታ ለሀገራችን ሰላም ምንም አይነት ፋይዳ የለውም። አዲስ አበባ የሁላችንም ማዕከል እና ፌደራላዊ ከተማ ሆና የሰላም ጉዞዋን አጠናክራ ትቀጥላለች። ከሀሰተኛ መረጃ ራሳችንን በማራቅ ለጋራ እድገታችን እና ለሰላማችን ዘብ እንቁም! ኢትዮጵያ በህዝቦቿ አንድነት ፀንታ ትኖራለች!