21/07/2026
ኢህአፓ ትግራይን በተመለከተ በተለያዩ ጊዜያት ያወጣቸው ሁለት ተቃራኒ አቋሞች ውዝግብ ፈጥረዋል!
-----
አውራምባ ታይምስ [አዲስ አበባ] - የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)፣ ዛሬ ሐምሌ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ፣ ገዥው የብልፅግና ፓርቲ የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ዋና መንፈስ በመጣስ የትግራይን ሕዝብ እንደገና ወደ ዳግም አውዳሚ ጦርነት ለመክተት ተግቶ እየሠራ ነው ሲል ክስ ሰንዝሯል። የፌደራል መንግሥት የትግራይን ሕዝብ የመንግሥት ሠራተኞች ደመወዝ፣ ነዳጅ፣ በጀት እና መሠረታዊ አገልግሎቶችን በመከልከል በ“ድምፅ አልባ ከበባ” ውስጥ አቆይቶታል ያለው ኢሕአፓ፣ አሁን ደግሞ ሕግ ማስከበር በሚል ሽፋን አዲስ ጦርነት ለመክፈት የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ እያካሄደ ነው ሲል ከሷል።
ይህ የኢህአፓ መግለጫ ዛሬ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ትልቅ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ መዋሉን ተከትሎ በትግራይ ልሂቃን ዘንድ የተወሰነ ድጋፍ ቢያስገኝለትም፣ በሌሎች የክልሉ ልሂቃን ዘንድ ግን ፓርቲው ቋሚ አቋም የሌለውና "ጊዜያዊ የፖለቲካ ሙቀትን ብቻ አስልቶ የሚራመድ" የሚል ትችትን አስተናግዷል። እነዚህ ተቺዎች ለዚህ እንደ ምክንያት የሚያነሱት ፓርቲው ከአምስት አመት በፊት ጦርነቱ ሲጀመር የያዘውን አቋም በዋቢነት በማንሳት ነው።
የአገር መከላከያ ሰራዊት በህዳር 19/2013 ዓ.ም መቐለን ሲቆጣጠር ኢህአፓ ባስተላለፈው የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት፣ "ጀግናው የመከላከያ ሰራዊታችን ታላቅ ተጋድሎ ፈጽሞ የጁንታው ቡድን ዋነኛ ምሽግ የሆነችውን መቐለ ከተማ መቆጣጠሩን ስንሰማ ደስታችን ወደር አልባ ሆኗል" ማለቱ ይታወሳል። እነዚህ ተቺዎች ይህንኑ የፓርቲው የቀደመ አቋም በማስታወስ አሁን ያራመደው አቋምስ በጊዜያዊ የፖለቲካ ሙቀት ያልተጋረደ ቋሚ አቋም መሆኑን እንዴት ማመን ይቻላል ሲሉ ጠይቀዋል።