23/02/2026
በሐዋሳ ከተማ በሁለተኛው ምዕራፍ የ8 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ ነው - የሐዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ
በሐዋሳ ከተማ በሁለተኛው ምዕራፍ የ8 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ በተሳለጠ ሁኔታ እየተከናወነ እንደሚገኝ የከተማዋ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሐዋሳ ከተማን በጎበኙበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት በከተማዋ እየተከናወነ ላለው የኮሪደር ልማት ትልቅ አቅምና መነሳሳትን የሚፈጥር መሆኑን ከንቲባው አክለው ተናግረዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በቅርቡ በሐዋሳ ከተማ በሁለተኛው ምዕራፍ የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎችን መጎብኘታቸው ይታወሳል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክት የኮሪደር ልማት ሥራዎች የተሻለች ሀገርን ለትውልድ የመገንባት አካል መሆናቸውንና በርካታ ከተሞችን እየለወጡ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡
የሐዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት በ8 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር መንገድ ላይ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት መሠረታዊ የሚባሉ አገልግሎቶችን ለኅብረተሰቡ ተደራሽ የሚያደርጉ መሠረተ ልማቶችን ያካተተ ነው።
ይህ የልማት ሥራ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ የነዋሪዎችን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል ያለመ መሆኑንም አብራርተዋል።
የከተማዋን የትራንስፖርት ፍሰት ለማሳለጥና የተሽከርካሪ መጨናነቅን ለመቀነስ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በዚህም የትራፊክ ፍሰትን የሚያቀላጥፉ 5 አዳዲስ የተሽከርካሪ ተርሚናሎች መገንባታቸውን ጠቁመው ከዚህ ቀደም በከተማዋ ያልነበሩ 13 ዘመናዊ የተሽከርካሪ ማቆሚያ(ፓርኪንግ) ቦታዎች መገንበታቸውንም ጠቁመዋል፡፡
ሐዋሳ የቱሪስትና የኮንፍረንስ ከተማ መሆኗን ያነሱት ከንቲባው፤ ለጎብኚዎችም ሆነ ለነዋሪዎች ምቹ የሆነ የእግረኛ መንገድ መዘርጋቱን ገልጸዋል።
በአጠቃላይ 17 ነጥብ 9 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የእግረኛ መንገድ መገንባቱን ጠቅሰው ከዚህ ውስጥ 2 ነጥብ 2 ኪሎ ሜትር የሚሆነው መንገድ እስከ 7 ሜትር የሚደርስ ስፋት ያለውና ለእግር ጉዞ እጅግ ምቹ ሆኖ የተሠራ ነው።
በአዲስ አበባ ከተማ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ለሐዋሳ ከተማ ትልቅ ልምድና ተሞክሮ መሆኑንም አቶ ጥራቱ ጨምረው ተናግረዋል።
ትላልቅ ፕሮጀክቶችን በጥራትና በአጭር ጊዜ ገንብቶ ማጠናቀቅ እንደሚቻል የታየበትን ይህንኑ ተሞክሮ በመጠቀም በሐዋሳም ሥራዎች በተሳለጠ ሁኔታ ተግባራዊ እየተደረጉ እንደሚገኙ አረጋግጠዋል።